(ዘ-ሐበሻ) በዛሬው ዕለት በቅሊንጦ ማረሚያ ቤት የተነሳውን የ እሳት ቃጠሎ ተከትሎ ፖሊስ በወሰደው እርምጃ 20 እስረኞች መገደላቸው ተሰማ:: በቅሊንጦ እስር ቤት አንጋፋ ፖለቲከኞች እና የሃይማኖት መሪዎች የታሰሩ ሲሆን የሟቾች ማንነት እስካሁን እንዳልተለየ ከአካባቢው የመጡ መረጃዎች አስታውቀዋል::
በሃገር ቤት የሚታተመው አዲስ ፎርቹን ጋዜጣም 20 ሰዎች ስለመገደላቸው የዘገበ ሲሆን 3 የ እሳት አደጋ ሰራተኞች ቆስለው ሃኪም ቤት ገብተዋል ብሏል::
በቂሊንጦ የተነሳው የ እሳት ቃጠሎ ሆን ተብሎ በ ስር ዓቱ የተከፈተ ነው የሚሉ አስተያየት ሰጪዎች አሉ:: እነዚህ አስተያየት ሰጪዎች እንደሚሉት ከዚህ ቀደም በተለያዩ ከተሞች የሕወሓት መንግስት ቦምቦችን በማፈንዳትና በ አልሸባብ በማሳበብ የውጪ ሃገራትን ድጋፍ ለማገኘት እንዳሴረ መዘገቡን አስታውሰው ባለፈው ሳምንት በሃረርጌ 2 መስጊዶች ላይ ቦምብ በመወርወርና ሰላማዊ ሰዎችን በመግደልና አሁን ደግሞ በቅሊንጦ ማረሚያ ቤት እሳት በማፈንዳት ከሽብርተኝነት ጋር በማያያዝ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ያቀደው ሊሆን ይችላል ይላሉ::
በቅሊንጦ ማረሚያ ቤት እንደነበቀለ ገርባ; እስክንድር ነጋና የመሳሰሉት ታዋቂ ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች የሚገኙ ሲሆን ስለደህንነታቸው ለማወቅ የተደረገው ጥረት አልተሳካም::
ጋዜጠኛ ኤሊያስ ገብሩ ከአዲስ አበባ የበቀለ ገርባ ባለቤትን አንገጋሮ እንደነበር በፌስቡክ ገጹ ዘግቧል:: የበቀለ ባለቤት ወሮ ሃና እንዳሉት ” በቀለም ሆነ ሌሎች በቂሊንጦ የሚገኙ እስረኞች በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ማወቅ አልቻልንም:: ከበቀለ ጋር ባሳለፍነው ሐሙስ ቂሊንጦ ተገናኝተን በሰላም ተነጋገረን ነበር። ትናንት ለጥየቃ መግባት አልቻልኩም። ዛሬ ልጃችን ቦንቱ ሄዳ ነበር። ረፋድ ላይ በቂሊንጦ በተነሳው ቃጠሎና ተኩስ ምክንያት ደውላለኝ ተነጋግረናል። ቀኑን ሙሉ በአከባቢው ብትገኝም አባቷን መጠይቅ ሳትችል ወደቤት ተመልሳለች። በቀለም ሆነ ሌሎች በቂሊንጦ እስር ቤት ያሉ ወገኖቻችን በምን ሁኔታ ላይ እንዳሉ ማወቅ አልቻልንም። ነገ እኔና ልጄ ቂሊንጦ እንሄዳለን።
