አንድ የሕዝብ እንቅስቃሴ ለመነሳት ምክንያት አለው፣ለመቆምም እንዲሁ።ብሶትና ምሬት የሕዝብን እምቢባይነት ይቀሰቅሳል።እንቅስቃሴው ከተሳካ በድል ይጠናቀቃል፤ አለዚያም በመንግሥት ሃይል የጥቃት እርምጃ ለጊዜው ሊገታ ይችላል። በዚህ መልክ የሚረጋገጥ የበላይነት ቂምን ስለሚወልድ ቅራኔውና ትግሉ እስከነአካቴው አይጠፋም።ጊዜ ጠብቆ ያገረሻል።ሌላው ምክንያት ደግሞ በመንግሥትና በተነሳው ሕዝብ መካከል ውይይት ተካሂዶ ሕዝቡ የሚፈልገውን እንደሚያገኝ የተስፋ ቃል ተሰጥቶትና ያንን ተቀብሎ ከተነሳበት እንዲያፈገፍግ የሚያደርግ ስራም ከተሰራ የሕዝብን ትግል ሊገታው ይችላል።
በኢትዮጵያ ውስጥ ላለፉት ወራቶች በተለያዩ ቦታዎች የተካሄደው ሕዝባዊ ትግል ገዥውን የወያኔ ቡድን እንዳርበተበተው የሚካድ አይደለም።ለዘጠኝ ወራት በኦሮሞው ኢትዮጵያዊ የተካሄደው ትግል ብዙ መስዋዕት ተከፍሎበታል።ሆኖም ግን ብዙ ሕይወት ከማስከፈሉ ውጭ የተገኘ ውጤት የለም።በቅርቡም በአማራው ማህበረሰብ በጎንደርና በጎጃም ውስጥ ብዙ ሕይወት የተከፈለበት ሕዝባዊ እንቅስቃሴ በባዶ እጅ ከመሰለፍ አንስቶ ነፍጥን ባካተተ መልኩ የመቋቋም ትግል በመካሄድ ላይ በመሆኑ ገዢውን ቡድን እስከዛሬ አይቶት ከማያውቀውና ካልጠበቀው የሕዝብ አመጽ ውስጥ ነክሮታል።ሕዝቡ መሞት ብቻ ሳይሆን መግደልም እንደሚያውቅ አሳይቶታል።በዚህም ምክንያት በስልጣን ላይ ያለው ቡድን ከውጭ አገር ወራሪ ጋር ከሚደረግ ጦርነት ባላነሰ ደረጃ በከባድ መሳሪያ የታጀበ የአገሪቱን የመከላከያ ሃይል ወደ ጎንደርና ጎጃም አዝምቷል፤ይህም ብቻ ሳይሆን የሱዳንን ወራሪ ጦር በእርዳታ እንዳሰለፈና በድንበር ከተማዎች ዙሪያ በመተማና በወልቃይት በአየር ሃይል ጭምር የጥቃት እርምጃ በመወሰድ ላይ እንዳለ በሰፊው ይነገራል።ጎን ለጎንም የተነሱበትን ሁለት ማህበረሰቦች ለማለያየት አንዱን በመቅረብ ሌላውን በማራቅ የስልት ጉዞ በማድረግ ላይ ይገኛል።
በዚህ የአገርን ክብር፣ ነጻነትና አንድነት በሚፈታተን ወረራ የወያኔ መሪዎች አጥፍቶ ለመጥፋት እንደቆረጡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተብየው አንደበት የተነገረው የጸረ ሕዝብና የእብሪት መግለጫ ያመለክታል።
በዚህ የሞት የሽረት ሕዝባዊ ትግል ሁሉም የአገሪቱ ዜጋ እጅ ለእጅ ተያይዞ የጀመረውን የነጻነትና የእኩልነት ትግል ከዳሩ ማድረስ ይገባዋል። በአማራው ኢትዮጵያዊ ዜጋ የሚካሄደውን የሕዝብ ትግል ለማኮላሸት ሃይማኖት አባቶች ታቦት ተሸክመው እንዲማጸኑ፣ የተደረገው ሙከራ ተቀባይነት ስላጣ ከሽፏል። ወጣቶችን በመግደል፣በማቁሰል፣ በጥርጣሬ ብቻ እያፈሱ በማሰር ፋታ ለመግዛት የታሰበው ስልትም አልሰራም።አሁን የተደረሰበት ውሳኔ የክተት አዋጅ በማወጅ በሃይል መደፍጠጥና የሕዝቡን ትግል እስከነአካቴው ማኮላሸት ነው።
በኦሮሞውም ህብረተሰብ በኩል የሚደረገውን ሕዝባዊ ትግል ለማኮላሸት ተመሳሳይ እርምጃዎች ተካሂደዋል።በመግደልና በማሰር የተደረገው ሙከራ አልተሳካም።ሁለተኛው ስልት በአዳማ ከተማ አዛውንቶችንና የአገር ሽማግሌዎችን በመሰብሰብ የአስታራቂ ሚና እንዲጫወቱ ማድረግ ነው።በሌላም ዙሪያ የተለያዩትን የኦሮሞ ድርጅቶች ሰብስቦ በማነጋገር ወደ አንድ የጋራ ጥቅም ወደ ሚያመራ ስምምነት ላይ የመድረሱ ሂደት መጀመር ነው።ይህ ስልት አሁን በአገር ውስጥና በውጭ አገር በመካሄድ ላይ ነው።የውጭ አገር መንግሥታትም በስልጣን ላይ ያለው አገልጋያቸው እንዳይወገድ ስለሚሹ የጥገና ለውጥ ተደርጎ እንዲቀጥል ምርጫቸው ነው።ያንን ደግሞ ለማሳካት በኦሮሞው ስም ከሚንቀሳቀሱትና የነሱም አጋር ከሆኑት ተቃዋሚ ነን ከሚሉት ቡድኖች ጋር ወያኔን ማስማማት ነው። እነዚህ ስምምነቶች ከዳር ከደረሱ፣ የአማራውን ማህበረሰብ ያገለሉና ለጥቃት አጋልጠው የሚሰጡ እንደሚሆኑ ግልጽ ነው። አሁን በመሬት ላይ ያለው ሃቅ የተጀመረውና ብልጭ ብሎ የታየው የኦሮሞና የአማራው ሕዝብ የመደጋገፍ የትግል አንድነት ሻማ እየከሰመ መሄዱ ከዚሁ አዝማሚያ የተነሳ መሆኑን ነው።በኦሮሚያ አካባቢ ላለፉት ዘጠኝ ወራት ሲካሄድ የነበረው የሕዝብ ትግል ጋብ ማለቱ የሚያመላክተው ነገር ቢኖር ይህንኑ ነው።አሁን ስርዓቱ በሚንገዳገድበት ወቅት የተቀጣጠለውን ትግል እንዳይበርድ በማድረግና መንግሥትን በየቦታው ወከባ ውስጥ በማስገባት ፈንታ በአማራው ላይ የጦር ሃይሉ ሲረባረብበት በዝምታ ማየት ወይም ከትግሉ ሜዳ ማፈግፈግ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ እንደማለት ይሆናል ሲተረጎምም የትግሬ መንግሥትና አማራው ሲዋጋ የሁለቱም ሃይል ሲዳከም በጎን የኦሮሞን ዘላቂ ፍላጎትን ማስከበር ይቻላል ከሚል ስሌት በመነሳት የተደረገ ውሳኔ ሊሆን ይችላል።
እውነት የኦሮሞ ድርጅቶች ጥቅማችንን በአማራው ኪሳራ ላይ እናስከብራለን ብለው የሚያስቡ ከሆነ ትልቅ ስህተት ንደፈጸሙ ሊያውቁት ይገባል።አማራው እስከመጨረሻው ድረስ ለህልውናውና ለኢትዮጵያ አንድነት ይቆማል፣ ይፋለማልም። ወያኔ ደግሞ አማራውን ካዳከመ በዃላ ኦሮሞውን ነጥሎ በተራው ይቀጠቅጠዋል እንጂ በእኩል ደረጃ የስልጣኑ ባለቤት አያደርገውም።በፊትም የታየው ይኸው ነው።ብልህ አንድ ጊዜ ብቻ ሊሞኝ ይችላል፤ደጋግሞ መሞኘት ከጅልነት በላይ ቂልነት ነው። አሁን ያለው አማራጭ አንድና አንድ ብቻ ነው።በኢትዮጵያዊነት እጅ ለእጅ ተያይዞ ከውጭ ሃይሎች ዘረፋና የነሱም ጉዳይ ፈጻሚ ከሆነው ዘረኛና ጨካኝ የወያኔ አገዛዝ ነጻ ለመውጣት ትግሉን በየቦታው እየተመካከሩ ማፋፋም። በድሉም የአንድ ነጻ አገር ባለቤት ሆኖ በእኩልነትና በነጻነት መኖር ። ሌላው ምርጫ ሳይሆን ፍርጃ ደግሞ የራሱን ቋንቋ በሚናገሩ አገር በቀል ሆዳሞች፣ ለውጭ አገር የእጅ አዙር አገዛዝ መሳሪያ በሆኑ አምባገነኖች መዳፍ ስር ወድቆ እያለቀሱ መኖር ይሆናል።
የማን ቤት ፈርሶ የማን ሊበጅ፣ እንረስ ካላችሁ ተስማምተን እንረስ፣ ያውሬ መፈንጫ ይሆናል እንጅ። የሁላችንም ቤት አንድ ላይ አይፍረስ።
የሚሉት አባባል በተግባር እንዳይገለጽ ብልህነትና ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል። አንዱ በሌላው ኪሳራ ላይ የሚኖርበት ወቅት አክትሟል።በአንድነት ተከባብሮና ተስማምቶ መኖር እንጂ ተለያይቶ በሰላም መኖር አይቻልም።
የኢትዮጵያን አንድነት የምትሹ ሁሉ የተቀጣጠለው ሕዝባዊ ትግል እንዳይሰናከል ተባበሩ፣ለትግሉም አስተዋጽኦ አድርጉ።ትግሉ ኢትዮጵያዊነትንና ኢትዮጵያን የማዳን ትግል ነው።በዚህ የትግል ዓላማ የሚስማማ የሁሉም ማህበረሰብ አባል ሊሳተፍበት ይገባል።
