አብዛኞቹ ሴቶች የሆኑ በሺዎች የሚቆጠሩ ተቃዋሚዎች በዋሽንግተን ዲሲ ከትራምፕ በዓለ ሲመት ቀድመው ተቃውሞ ለማሰማት አደባባይ ወጥተዋል። የተመራጩ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በዓለ ሲመት ከመካሄዱ በፊት የተካሄደው ተቃውሞ ከ2017 ጀምሮ የተከናወነ ነው። መጀመሪያ መጠሪያው ‘ዉሜንስ ማርች’ የነበረ ሲሆን አሁን ‘ፒፕልስ ማርች’ ተብሏል። የትራምፕን ዕሳቤ ወይም ትራምፒዝም ለመቃወም አደባባይ እንደወጡ በድረ ገጻቸው ተጽፏል። በኒው ዮርክና ሲያትልም የተቃውሞ ሰልፎች ተካሂደዋል። በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት ትራምፕ በሚያከናውኗቸው ሥነ ሥርዓቶች ተቃውሞዎቹ ጣልቃ ይገባሉ። ቅዳሜ ዕለት 50,000 ሰዎች ይገኛሉ ተብሎ ቢጠበቅም 5,000 የሚሆኑ ተቃዋሚዎች ናቸው የተገኙት። በሦስት ፓርኮች ተቃዋሚዎቹ ተሰባስበው ወደ ሊንከን ሜሞሪያል አቅንተዋል። “የተለያየ ማንነት ያላቸውና የተለያየ ፍላጎት ያላቸው” ተቃዋሚዎች መሆናቸው የተገለጸ ሲሆን፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የሴቶች መብት እና የስደተኞች መብት ካነሷቸው ጉዳዮች መካከል ይጠቀሳሉ። ከዚህ ቀደም አምባገነኖችን ለመቃወም ጥቅም ላይ የዋሉ መንገዶችን ተጠቅመው ትራምፕን መገዳደር እንደሚፈልጉ ተቃዋሚዎቹ ገልጸዋል። የተወሰነ ቁጥር ያላቸው የትራምፕ ደጋፊዎችም በዋሽንግተን ሞኑመንት ተገኝተዋል። አሜሪካን ዳግመኛ ታላቅ እናድርግ የሚል ኮፍያ አድርገው የታዩ ሲሆን በተቃራኒው ተቃዋሚዎች ‘ኖ ትራምፕ ኖ ኬኬኬ’ የሚል መፈክር እያሰሙ ተገኝተዋል። ትራምፕን ለመደገፍ ከወጡት መካከል አንዱ ቲሞቲ ዌልስ ተቃዋሚዎቹ ድምጻቸውን ማሰማት “መብታቸው ነው። ግን እንደ አገር ያለንበት ሁኔታ ያሳዝናል” ብሏል። ተቃውሞው የተጀመረው ሂላሪ ክሊንተን በትራምፕ ሲሸነፉ ነው።

ከዲሲ ባሻገር በሌሎች ከተሞችም ተቃውሞው የቀጠለ ሲሆን ሴቶች ትራምፕን በመቃወም ድምጻቸውን ማሰማት ቀጥለዋል። ትራምፕ ለበዓለ ሲመታቸው ዲሲ ገብተዋል። የትራምፕ ተቃዋሚ የሆነችው ብሩክ “ከዚህ ቀደም ውድቀቱን ያየነውን ሰው ደግመን በአገራችን በመምረጣችን አዝናለሁ። ለሴት እጩ ዕድል መስጠት አልቻልንም” ብላለች። ሌላዋ ተቃዋሚ ከይላ “አዝኛለሁ። ተበሳጭቻለሁ” ስትል አስተያየቷን ሰጥታለች። ከእህቷ አን ጋር ለተቃውሞ ከሳን ፍራንሲስኮ ዲሲ የሄደችው ሱዚ “አሁን ትራምፕ የበለጠ ጀግንነት እየተሰማው ነው። ቢልየነሮችም እየደረፉት ነው” ብላለች። ሌላ ሴት ተቃዋሚ በበኩሏ “አሁንም አለን። መቃወም እንቀጥላን” ስትል ተናግራለች።